አቡነ ተክለሃይማኖት

 ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት

 ዘኢትዮጵያ አቡነ ተክለሃይማኖት

፲፱፻፷፰ -፲፱፻፹

ቡነ ተክለ ሃይማኖት ከጵጵስናቸው በፊት መጠሪያ ስማቸው አባ መልአኩ ሲሆን የተወለዱት መስከረም 10 ቀን 1910 ዓ.ም የንጉስ ወልደ ጊዮርጊስ ታማኝ ወታደር ከነበሩት አባታቸው ከወታደር ወልደ ሚካኤል አዳሙ እና አባታቸው ለውትድርና ጎጃም ሄደው ካገቧቸው ባለቤታቸው ከወይዘሮ ዘውዲቱ ካሣ በጎንደር ጠ ቅ ላይ ግዛት “ማኅ ደረ ማርያም” ተብላ በምትታወቀው ገዳም አካባቢ ጋዥን በምትባል ቦታ ነው።

አባታቸው ወታደር ወልደ ሚካኤል ባደረባቸው ህመም ልጃቸው አባ መልአኩ ገና እርጥብ አራስ እያሉ በሞት ከዚህ አለም ተለዩ። በዚህም የተነሳ እናታቸው ወይዘሮ ዘውዲቱ ልጃቸው አባ መላኩ ትንሽ ጠንከር ሲሉ ይዘዋቸው ተመልሰው ወደ ጎጃም ተመለሱ እና አባ መልአኩ እዚያው ጎጃም ውስጥ ዘርዘር ሚካኤል በሚባል አካባቢ ማደግ ጀመሩ። ነገር ግን ብዙም የመጀመሪያ ትምህርታቸውን እንደጀመሩ እናታቸውም በሞት ከዚህ አለም ይለዩና ተመልሰው የአባታቸው ዘመዶች ወደሚገኙበት ቦታ ወደ ጎንደር ተመለሱ። ዘመዶቻቸውም እዚያው አካባቢ ተዋቂ መምህር ለነበሩት መሪ ጌታ ወርቅነህ ሠጧቸው። በዚያም ፊደል ከቆጠሩ በሇላ ወደ ደብረ ታቦር ተሻግረው እናቲቱ ማርያም በተባለችው ደብር ያስተምሩ ከነበሩት አለቃ ቀለመወርቅ ዘንድ ሔደው የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቀቁ። ከዚህም በሇላ ወደ አዲስ አበባ መጥተው በወቅቱ የኢትዮጵያ ጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ መዓረገ ዲቁናን ተቀበሉ። ከዚያም ወደ ማኅደረ ማርያም ተመልሰው በዲቁና ሲያገለግሉ ቆዩ።


አባ መልአኩ ህይወታቸው በቤተ ክርስትያን ትምህርት አጎልምሰው በትኅርምትና እግዚአብሔርን በህይወታቸው ሙሉ በማገልገል ሊኖሮ በመወሰን ከጏደኞቻቸው ጋር ቅኔ ለመማር ወደ ጎጃም ይሄዳሉ። በዚያም በእናታቸው ሃገር አጠገብ ወደሚገኘውና የረዝ ሚካኤል ወደ ተባለው ቦታ መምህር ልሳነ ወርቅ ከተባሉ መምህር ዘንድ ቅኔንና ዜማን ለስምንት አመታት ያህል ተማሩ።

የዜማውንና የቅኔውን ትምህርት በሚገባ ካጠናቀቁ በኋላ በተማርኩት ደግሞ ጥቂት ላገልግል በማለት ወደ ደብረ ታቦር ሔዱ። ይሁን እንጂ ወዲያውኑ የኢጣልያ ፋሺስት ጦር ኢትዮጵያን በግፍ በመውሪሩ እንዳሰቡት በሰላም ሊያገለግሉ አልቻሉም፡፡ በመሆ ኑም የአገልግሎት አሳባቸውን በመተው ራቅ ወዳለ ቦታ ሔደው በብሕትውና እየኖሩ ለመማር ወሰኑ፡፡ ይህንን ውላኔያቸውን ተግባ ራዊ ለማድረግ የሚሔዱበትን ሀገር ለመወሰን ሲያወጡ ሊያወርዱ እና የጓደኛቻቸውን ምከር ሲጠይቁ አንድ ጓደኛቸው በደቡብ ኢትዮጵያ ወላይታ አካባቢ አጎቱ በመንግሥት ሥራ ተሠማርቶ እንደ ሚኖርና አካባቢው በ13ኛው ክፍለ ዘመን ጻድቁ አቡነ ተከለ ሃይማኖት የተጋደሉበት፣ እንደ ደብረ መንክራት አቡነ ተከለ ሃይማኖት ዓይነት ታላላቅ ገዳማት እንዳሉበት፣ ቦታው በጥምቀት የቅድስት ሥላሴን ልጅነት ያላገኙ ሰዎች የሚበዙበት በመሆኑ ለብሐትውናና ለአገልግሎት የሚመች መሆኑን መክሮ አብረው ቢሔዱ ለጊዜው አጎቱ ቢት አንደሚያርፉ ይነግራቸዋል፡፡ ቅዱስነ ታቸውም የጓደኛቸውን አሳብ ተቀብለው በ1926 ዓ፡ም ሁለቱም ወደ ወላይታ ጉዞአቸውን ጀመሩ፡፡

አድካሚ ከሆነው ከብዙ ቀናት የእግር ጉዞ በኋላ ወላይታ ደርሰው ከጓደኛቸው አጎት ቤት ዐረፉ፡፡ አካባቢውን እስከሚላመዱ በእንግድነት ከቆዩ በኋላም ዝናው ከጎንደር ስቦ ወዳስመጣቸው ደብረ መንከራት አቡነ ተከለ ሃይማኖት ገዳም ገቡ፡፡ እግዚአብሔር እንደነ ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስና ጻድቁ አቡነ ተከለ ሃይማኖት በአካባቢው ሥራ እንዲሠሩ መርጧቸዋለና ወደ ገዳሙ ሲገቡ በቦታው ረዘም ላለ ጊዜ የቆዩትን አለቃ ደስታ የተባሉትን ባሕታዊ አገኙ፡፡ ከእሳቸ ውም ጋር በአንድ በአት ተወሰነው መኖር ጀመሩ።ይቀጥላል


“ማድረግ የምትችሉት እኔን ገድላችሁ ነው!!” አቡነ ተክለሃይማኖት

እዚያ ቦታ ላይ መገኘታቸው አባ መልአኩን ግራ አጋብቷቸዋል። እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ በመንበረ ፓትሪያርኩ ጊቢ አብረዋቸው በአንድ ክፍል እንዲዳበሉ እና እንዲጠብቋቸው ትእዛዝ የተሰጣቸው አባ ገ/ሚካኤልም ግራ ተጋብተዋል። ጥቂት ቀናት እንደተላመዱም እንዲህ ሲሉ ይጠይቋቸዋል።

“አባቴ ከየት ነው የመጡት!?” ይሏቸዋል አባ ገ/ሚካኤል።

“ከወላይታ ሶዶ።”

“ከእዚያ ምን ያደርጋሉ?”

“አስተምራለሁ።”

“ምን ያስተምራሉ?”

“መንፈሳዊ ትምህርት ነው፤ ወንጌል አስተምራለሁ።”

“ታዲያ አሁን ወደዚህ የመጡት ለምንድነው?”

“የመጣሁትማ ጠርተውኝ ነው።”

“ማነው የጠራዎት?”

“ቅድም ያመጡኝ ሰዎች ናቸው…ከእሳቸው ጋ ቆይ ያሉኝ።”

“ለምን ጉዳይ ነው የጠሩዎት?”

“አላውቅም።”

እኚህ አባት በትክክልም ለምን እንደተገኙ አያውቁም። እንዳውም እሳቸውን ያሳዘናቸው የብፁ አቡነ ቴዎፍሎስ በነበረው መንግስት መታሰር ነበር።

አባ መልአኩ ምክንያቱን በማያውቁት ጉዳይ ቆዩ መባላቸው ስልችት ብሏቸዋል። እና አንድ ቀን ጠባቂያቸው ወደጎረቤት ሄድ እንዳሉ እሳቸው ጊቢውን ጥለው ሄዱ።

ጠፉም ተባለ። የደርግ ደህንነቶች ፍለጋውን አጧጧፏት። ባህታዊው ቢጫ ሸማቸውን እንደተከናነቡ፣በባዶ እግራቸው፣ እግራቸው ወዳመራቸው ሲገሰግሱ ተያዙ።

እንግዲህ እኚህ መሾማቸውን ያላወቁ አባት ነበሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ሆነው የተሾሙት፤ብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖት።

በተሾሙ ጊዜም ሹመቱን አልቀበልም፣ “መንበሩ ለእኔ አይገባም!” ብለው ነበር። አምርረውም አልቅሰዋል። እንዳይሰወሩም ጥበቃ ተሰማርቶባቸው ነበር።

አንድ ለመውጫ፥

የወቅቱ መንግስት ኮሚኒስት ነውና ብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖትን መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያንን አስመልክቶ ያናግሯቸዋል፥

“…አባታችን ይህንን ካቴድራል ወደ ሙዚየምነት ልንቀይረው እንፈልጋለን። ሌላ አለም ላይ እየተለመደ የመጣ ነው። ቤተ እምነቶች ወደ ሙዚየምነት እየተለወጡ ነው። እኛም አስበናል!” ይሏቸዋል።

እሳቸውም ድፍረታቸው እያስደነቃቸው፥

“ታዲያ ምን ችግር አለ። ትችላላችሁ! …ግን ያንን ማድረግ የምትችሉት እኔን ገድላችሁ ነው!!” ብለዋል።

በነገራችን ላይ ብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖት አብዝተው የሚጾሙ እና የሚጸልዩ ነበሩ። ከእዚህ ምድር በድካም ሲያልፉም የሰውነት ክብደታቸው 25 ኪሎ ደርሶ ነበር።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በየዘመናቱ እንደተፈተነች ነው። የገዛ ልጆቿ፣ አገልጋዮቿ ሳይቀር እንደይሁዳ አሳልፈው ሰጥተዋት ያውቃሉ። ግን ሁሉንም አልፋ ዘመናትን ስትሻገር ነው የምትገኘው።

በረከታቸው ይደርብን።